የሱዳን ሰራዊት በህግ ወጥ የሰዉ አዘዋዋሪዎች የተያዙ 29 ታጋቾችን አስለቀቀ
TMP – 04/03/2017
በለካቲት 21 የሱዳን ብሔራዊ የደህንነትና ጸጥታ ሃይሎች በህገወጥ የሰዉ ንግድ አዘዋዋሪዎች ቡድን ሚደሲሳ በተባለ የክሰላ ግዛት ተይዘዉ የነበሩ 29 ታጋቾችን አስለቅቋል፡፡
“ታጋቾቹ የተገኙት በብረት አጥር እና ለጤናቸዉ አደገኛ በሆነ ቦታ ነዉ” ያሉት የሰራዊቱ አዛዥ ሻለቃ አብዱል ከሪም አብደልዳፊ ይህ ህገወጥ የሰዉ ንግድ አዘዋዋሪዎችን የመከላከል አንዱ አካል መሆኑን ገልጸዉ “3 የህገወጥ ቡድኑ አባላትም በቁጥጥር ስር ዉለዋል” ሲሉም ተናግረዋል፡፡
እንደ ሱዳን የዜና አገልግሎት ዘገባ ከሆነ ከታጋቾቹ 8ቱ ሴቶች ሲሆኑ ከባድ የተኩስ ልዉዉጥ በተካሄደበት ዘመቻ አንድ የሱዳን ብሄራዊ የደህንነት እና ጸጥታ ኃይል አባልም ቆስሏል፡፡
አልታሪቅ የተባለ ጋዜጣ ባለፈዉ ሳምንት 1500 ኤርትራዉያን፣ ሶማሊያዉንና ኢትዮጵያዉያን ስደተኞች በምስራቃዊዉ የሱዳን ከሰላና ገዳሪፍ ግዛቶች ገለ በተባለ ቦታ መታገታቸዉ ዘግቧል፡፡
ሱዳን በህገወጥ የሰዉ ንግድ የተሰማሩ አዘዋዋሪዎች መፍለቂያና ማስተላለፊያ አገር በመሆንዋ ከ2014 ጀምሮ እነዚህን ህገወጥ ቡድኖች ለማጥፋት ጠንካራ እርምጃ እየወሰደች መሆንዋና የሱዳን ፓርላማም ጸረ–ህገወጥ የሰዉ ንግድ ዝዉዉር አዋጅ ያጸደቀ ሲሆን በዚህ ህገወጥ ተግባር የተገኘም እስከ 20 ዓመት እስራት ይፈረድበታል፡፡
ዓለም አቀፉ ማህበረሰብም ይህንን የሱዳን ጥረት እየደገፈዉ ሲሆን የአዉሮፓ ህብረትም ህገወጥ አዘዋዋሪዎችን ለመግታት ለምታደርገዉ ጥረትና በዚያች ሃገር የሚገኙ ስደተኞችን ኑሮ ለማሻሻል የ100 ሚሊዩን ዩሮ በጀት መመደቡ ይታወቃል፡፡
በተጨማሪም ሃገሪቱ ከአዉሮፓ ህብረት የኣስቸኳይ ጊዜ እርዳታ ድጋፍ ለአፍሪካ የ40 ሚሊዮን ዩሮ ተጨማሪ ገንዘብ በአካባቢዉ ያለ ስደትን ለመቆጣጠር የሚዉል ድጋፍ ማገኘቷ ተገልጿል፡፡
ፅሑፉን ያካፍሉ